እንኳን ለእመብዙሃን ቅድስት ድንግል ማርያም አመታዊ ክብረ በዓል አደረሳችሁ ግሸን ማርያም
Автор: YEMENZ WERK YOU TUBE የመንዝ ወርቅ ቲዩብ
Загружено: 2025-10-01
Просмотров: 122
🕊 ግሸን ማርያም፣ ደብረ ነጎድጓድ፣ ደብረ ነገሥት፣
ደብረ ከርቤ
እንኳን አደረሳችሁ
አምላክ አስቀድሞ ምድሯን አሳመራት፣ በመስቀል ቅርጽ አስዋባት፣ ስሙ እንዲጠራባት፣ ክብሩ እንዲነገርባት፣ ሕዝብ እንዲሰበሰብባት፣ ቅዱሳን እንዲኖሩባት፣ ትውልድ ሁሉ ጥበብን እንዲማርባት፣ ስሟን እየጠራ እንዲፈልጋት አዘጋጃት፤ በቅድስና ስትጠበቅ ኖረች፣ የቅዱሳን መዳረሻ ኾነች፣ የረቀቀውን ያዘች፡፡
መልካሙ ማዕዛ ሲያጥናት ኖረ፣ የአምላክ ስም ከበረ፡፡ አበው በልባቸው አሰቧት፣ መንነው ተጓዙባት፣ በአጸዷ ሥር ተሰባሰቡባት፣ ስለ ሰው ልጆች ሰላምና ደስታ፣ ፍቅርና አንድነት ጸለዩባት፣ ምድር በበረከት ትሞላ ዘንድ ተማፀኑባት፡፡ ምድር በማዕት እንዳትጠፋ አምላክን አብዝተው ለመኑባት፣ አምላክም ጸሎታቸውን ሰማቸው፣ ምድሯን እየባረከና እየቀደሰ አኖራቸው፡፡
ዓለም የዳነበት፣ ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበት፣ የጨለማው ዘመን የተገፈፈበት፣ ብርሃን የበራበት፣ ሰውና መላእክት በአንድነት የዘመሩበት፣ ሰማይና ምድር የታረቁበት፣ የሲኦል ደጆች የተጨነቁበት፣ ክርስቲያኖች መመኪያ የሚያደርጉት፣ ጥልን የሚገድሉበት፣ ሰይጣንን የሚያርቁበት፣ መንፈስ ቅዱስን የሚያቀርቡበት፣ የሚባረኩበት፣ የሚቀደሱበት፣ ከሞት የዳኑበት መስቀል አረፈባት፡፡
የደቡብ ወሎዋን መዲና ደሴ እንደ ደረሱ 82 ኪሎ ሜትሮችን በስተሰሜን አቅጣጫ እንደሄዱ ግሸንን ያገኛሉ፡፡ የብዙዎችን ቀልብ የሚስበው፣ ባስደማሚ መልከዓ ምድር ላይ የሚገኘው ገዳም ያለውም ከዚያ ከመስቀለኛው ተራራ ላይ ነው፡፡
ገዳሙ ግሸን ደብረ ከርቤ ይባላል፡፡ ከከፍኛው ተራራ ላይ እንደደረሱ ከሃይማኖታዊ ክዋኔው ባለፈ ዙሪያ ገባውን ሲመለከቱት ከአግራሞት ላይ ሌላ አግራሞትን የሚፈጥሩ ድንቅ መልከዓ ምድሮችን ይቃኛሉ፡፡ የአምባው ዙሪያ እንደምሰሶ ቀጥ ባሉ የመሬት ገጽታዎች የተከበበ ነው፡፡ ከላይ ሆነው ወደታች ሲመለከቱት ዙሪያውን ባለው ሰንሰለታማ ተራራ ይደመማሉ፡፡ በዚያች ለመውጫ እና ለመውረጃ ከምታገለግለዋ ተፈጥሮ ካዘጋጀቻት አንዲት ጠባብ መንገድ ውጪ ሌላ አማራጭ መንገድ የለም፡፡
ጠባቧ መንገድ በአጼ ኃይለሥላሴ ዘመነ መንግሥት በጠፍጣፋ ድንጋይ የመወጣጫ ደረጃ ከመሰራቱ በፊት ወገባቸውን በገመድ ወይም በመጫኛ ታስረው ነበር የገዳሙ መነኮሳት አምባውን የሚወጡትም ሆነ የሚወርዱት፡፡ በአምባው ላይ በተለያዩ ጊዜያት የተተከሉ አራት አብያተ ክርስቲያናት ይገኛሉ፡፡
መስቀሉ በመስቀለኛው ተራራ ተቀመጠባት፡፡ ከመስቀለኛው ተራራ አናት ላይ ቅዱሳን ይኖሩባታል፣ የአምላክ ስም በሰርክ ይጠራባታል፣ ጥበብ ይገለጥባታል፣ እውቀት እንደ ዥረት ይፈስስባታል፣ እጅግ ያማረው ማዕዛ ያውዳታል፣ መንፈስ ቅዱስ ይጠብቃታል፣ ከፍ ከፍም ያደርጋታል፡፡
እርሷ የያዘችው ሀገራት እንዲኖራቸው የተመኙትን፣ የእነርሱ ያደርጉት ዘንድ የታተሩበትን ነው፡፡ እርሷ አስቀድማ ተመርጣለች እና መስቀሉ ተቀመጠባት፣ መንፈስ ቅዱስ መላባት፣ ጻድቃን ተሰባሰቡባት፣ ምዕመናን ከበረከቷ ይካፈሉ ዘንድ አውራጃዎችን እያቆራረጡ ተጓዙባት፣ ዳገቱ ሳያደክማቸው፣ እሾህና አሜካላው ሳይበግራቸው፣ የረቀቀ ታሪኳን፣ የከበረ ስሟን እያነሱ ተመላለሱባት፡፡
እግዚአብሔር አስቀድሞ ያዘጋጃት እና የመረጣት አምባ ይሏታል፣ በተመረጠችውም አምባ ይሰባሰቡባታል፣ የአምላካቸውን ስም በጋራ እያነሱ በጋራ ይጸልዩባታል ግሸን ደብረ ከርቤ፡፡
ከሀገረ እስራኤል ኢየሩሳሌም የሮማውያንን ክፉ በትር የሸሹ አበው በየመን በሀገረ ናግራን ይኖሩ ነበር። በዚያ ምድር ዓለምን ንቀው የሰማዩን ርስት የሚሹ አንድ ጻዲቅ መነኩሴ ይኖሩ ነበር። እኒያም ሰው የቀደመ ስማቸው ፍሊክስ የኋለኛው ስማቸው ደግሞ ፈቃደ ክርስቶስ ይባሉ ነበር። ከቅዱሱ መናኙ ጋርም ሁለት ጽላቶች ነበሩ፣ የእግዚአብሔር አብና የቅድስት ድንግል ማርያም። እኒያ የበቁ አበው ሁልጊዜም አምላካቸውን እያመሰገኑ ይኖሩ ነበር፡፡ ያለ ጸሎትና ምልጃ ውለው አያድሩም፣ ከእለታት በአንድ ቀን ለእኒያ ደግ ሰው መልካም ነገር ታያቸው፡፡ ማርያም ለቅዱሱ አባት በራዕይ ተገለጠችላቸው። ጽላቶቹን ይዘው የብርሃን ምሰሶ ተተክሎ ወደሚታይበት፣ ሀገር ይሄዱ ዘንድ ነገረቻቸው። የተባሉትን አደረጉ። በራዕይ የተነገራቸው ሥፍራም የአምላክ ስም ለዘለዓለም የሚመሰገንበት፣ ቅዱሳን አበው የሚኖሩበት፣ መላእክት የሚጠብቁት ነው፡፡
አባ ፈቃደ ክርስቶስ መነኮሳትን አስከትለው በራዕይ ወደታዬቻቸው ምድር ገሰገሱ። በመንገዳቸውም የእግዚአብሔር መላክ ይመራቸው ነበር፡፡ አስቀድሞ ከተነገራቸው የብርሃን አምድ ከተተከለባት ምድር ደረሱ። የብርሃን አምድ ተመለከቱ፡፡ ፈቃደ ክርስቶስ የበሽሎን ወንዝ ተሻግረው ወደ ተራራው አቀኑ። ተራራው ከሁሉም ተራራዎች ይለያል። ወደላይ ሊወጡ ሲሉ ገደሉን ንብ ሠፍሮበት ነበር። የንቡ ብዛት የማሩ ሰፈፍ ያስደነቃቸው ቅዱሱ መናኝ ይህስ አምባአሰል ነው አሉ። አሰል ማለት በአረበኛ ማር ነው። የማር አምባ ሲሉ አምባሰል አሏት። በመስቀል የተቀረጸ ምድር፣ የመናንያን፣ የባሕታዊያን የቅዱሳን፣ የበረከት ሀገር አምባሰል። ፈቃደ ክርስቶስ ወደ ተራራው የምታስወጣቸው አንዲት መንገድ አግኝተው ተከታዮቻቸውን አስከትለው ወደ ተራራው ወጡ። በዚያም ቤት ሠርተው እንደታዘዙት ሁለቱንም ጽላቶች በመስቀለኛው ተራራ ላይ አስቀመጧቸው። ይህችም ሥፍራ ግሸን ደብረ ከርቤ፣ ግሸን ማርያም ናት፡፡
በዚያ ዘመንም በመስቀለኛዋ ተራራ ቤተመቅደስ ታነጸ። የብርሃኑ አምድም በክብር ኖረ፡፡ ቤተ መቅደሱን አከበሩ።
የሰማይ መላእክት፣ ስውራን አባቶች በዚያች አስቀድማ በተመረጠች ስፍራ አምላክን ያመሰግኑባት፣ ሕገ እግዚአብሔርንም ይተገብሩባት ነበር ነው ያሉኝ፡፡ አባ ፈቃደ ክርስቶስ የእግዚአብሔር መላእክ እንደነገረኝ እና እንደ መራኝ ይህች ቦታ ትክከለኛዋ ቦታ ናት በማለት ቤተ መቅደስ ያነጹባት፣ ታቦታትንም በክብር ያስቀመጡባት፣ ራዕያቸው እውን የሆነባት የከበረችና የተቀደሰች ሥፍራ ናት፡፡
የማር አምባ የሆነችው፣ በመስቀለኛ ተራራ ያረፈችው፣ አስቀድማ የተመረጠችውና የተጠበቀችው ግሸን ደብረ ከርቤ የበዙ ምስጢራት ባለቤት ናት፡፡ ዘመን ነጎደ፡፡ ነገሥታቱ በዙፋኑ ላይ እየተተካኩ ማስተዳደራቸውን ቀጠሉ፡፡ የአፄ ይኩኑ አምላክ ዘመን በደረሰም ጊዜ ወደ ግሸን አምባ ሄዱ፡፡ ስፍራዋም እጅግ ያማረችና የተዋበች ነበረችና ወደዷት፡፡ ለቤተ መንግሥትም ለቤተ ክህነትም ትሁን አሉ፡፡ ስሟም ደብረ ነጎድጓድ ትባል፣ የማርያም ጽላትም ከአግዚአብሔር አብ ወጥታ ለብቻዋ ደብር እንዲደበርላት አደረጉ ።
እርሷም የቤተክህነት እና የቤተ መንግሥት ሰዎች የሚወጡባት ኾና ኖረች፡፡ ለቤተክህነቱ ጳጳሳቱ፣ ካህናቱ፣ ዲያቆናቱ፣ መነኮሳቱ፣ ለቤተ መንግሥት ነገሥታቱ፣ መኳንንቱ፣ መሳፍንቱ ወጡባት
ንጉሥ አልፎ ንጉሥ ተተክቶ በምድሯም አጼ ዘርዓያዕቆብ በአባታቸው ዙፋን ላይ በተቀመጡ ጊዜ ከአባታቸው ዙፋን ጋር የተቀበሉት የከበረ ቃል ኪዳን ይፈጽሙ ዘንድ ተነሱ፡፡ መስቀሌን በመስቀለኛ ቦታ አኑር የሚል ቃል ተነግሯቸው ነበርና ከአባታቸው የተቀበሉትን መስቀል የት እንደሚያኖሩት ማንሰላሰል ጀመሩ፡፡ የተነገሩትን ምስጢራዊ ቃል ለመተግበር ግን ቀላል አልነበረም፡፡ መድከምን፣ በቅዱሳን መመራትን፣ ምስጢር መፍታትን ይጠይቃልና፡፡ አምላክ አግዟቸው የተባሉትን በክብር አደረጉ፡፡
ይህች ሥፍራ መስቀሌን በመስቀለኛ ቦታ አኑር በተባለው ቃል መሠረት መስቀሉ ያረፈባት፣ የከበሩ ንዋዬ ቅድሳት ያሉባት ናት፡፡ በዚህችም የከበረች ሥፍራ ምዕመናን ይሰባሰቡባታል፡፡ ግሸን ደብረ ከርቤ ምዕመናን አምላካቸውን የሚያመሰግኑባት፣ ስለ ሀገራቸውና ስለራሳቸው የሚማጸኑባትና የእግዚብሔር ቸርነትና በረከት የበዛባት ሥፍራ ናትም ።
ከዓጼ ዘርዓ ያዕቆብ ዘመነ ንግሥና ጀምሮ ኢትዮጵያዊያን ግማደ መስቀሉን ሊሳለሙ፤ የጌታን እናት ሊማጸኑ በየዓመቱ በዚህ ወቅት ወደ ግሸን አምባ ያቀናሉ፡፡
እንደ ዛሬው የትራንስፖርት አማራጮች ሳይሰፉ ጥንት ኢትዮጵያዊያን አድካሚውን የእግር ጉዞ በብርታት፤ ፈታኙን የአምባ ላይ ጉዞ በጽናት አጠናቅቀው ከአምባው ጫፍ ላይ ሲደርሱ ሃሴታቸው ምድራዊ ብቻ ሳይኾን ሰማያዊ በረከትም አለው ተብሎ ይታመናል፡፡ የሚረግጧት ምድር የክርስቶስ ግማደ መስቀል በክብር ያረፈባት እና የተመረጠች መስቀለኛ ቦታ ናት፡፡ ይህንን ክብር የግብጿ አሌክሳንድሪያ ተመኝታው አልተሳካላትም፤ ፋርስም ይህ እንዲኾንላት ፈልጋ አልቻለችም ነበር፡፡
በሐይቅ እና መቅደላ፤ በደላንታ እና በየጁ መካከል የምትገኘው የግሸን አምባ የበሽሎ ወንዝ አዋሳኟ ነው፡፡ የአምባሰል ሰንሰለታማ ተራሮች ለክብሯ ዘብ የቆሙላት ግሸን የበሽሎ ወንዝ ዘመናትን እንደ ጅረት የፈሰሰው ውበቷ የሚቀዳበት ወንዝ ነው፡፡ ተለያየን ወደ ግሸን የሚያቀኑ ምዕመናን ከድካማቸው አርፈው፤ ላበታቸውን አለቃልቀው ፋታ የሚያገኙበት የአካባቢው ጸጋ ተደርጎ ይወሰዳል፡፡
ግሸን ደብረ ከርቤ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ እምነት ተከታዮች ዘንድ በአንጋፋነታቸው ከሚታወቁት ቅዱሳን ሥፍራዎች አንዷ ናት፡፡ የእምነቱ ተከታዮች እንዲሁም ሌሎች የገዳሟን ታሪክ ማወቅ የሚፈልጉ ሰዎች በየጊዜው ወደ ግሸን ይጓዛሉ፡፡
የእመቤታችን
Доступные форматы для скачивания:
Скачать видео mp4
-
Информация по загрузке: