ጎንደር
Автор: ዜብራ ሌንስ
Загружено: 2025-04-11
Просмотров: 94
የጎንደር ታሪክ በተመራማሪው ዓይን
በ1623 ሰኔ ወር ላይ አፄ ሱንስዮስ ለልጃቸው ለአፄ ፋሲል በህይወት እያሉ ስልጣናቸውን ያስተላልፋሉ፡፡ ፋሲል ስልጣናቸውን ተቀብለው አፄ ከተባሉ ከ4 ዓመታት በኋላ አሁን ቤተመንግስታቸው ከሚገኝበት ቦታ መጥተው የዛሬዋን ጎንደር ሊመሰርቱ ችለዋል፡፡
አሁን ቤተ መንግሥቱ ያለበት ቦታ 2200 ሜትር ከባህር ጠለል በላይ ከፍታ አለው፡፡ ዙሪያውን ደግሞ እስከ 3 ሺህ ሜትር ከፍታ ያላቸው ተራራዎች አሉ። እነዚህ ተራራዎች የአየር ወለድ በሽታ ቢመጣ ወደ ከተማዋ አያስገቡም/አያሳልፉም ተብሎ ይታሰባል፡፡ ከጦር ስትራቴጂ አንፃርም በተራራ መከበቧ ጠላት በቀላሉ እንዳይገባ ይከላከላል፡፡ ተራራዎቹ በትልልቅ ዛፎች የተጠቀጠቁ መሆናቸውም የማገዶ ፍጆታን ያሟላሉ፡፡ በእነዚህና በሌሎች ምክንቶች ጎንደር በ1628 ዓ.ም ተመሰረተች፡፡
አፄ ፋሲለደስ በ1660 ዓ.ም ከዚህ ዓለም በሞት ሲለዩ፣ የጎንደር ህዝብ ብዛት 27 ሺህ ደርሶ ነበር። ይሄ የሚያሳየው ከተማዋ በወቅቱ እጅግ ሰፊ መሆኗን ነው፡፡ በእነ እቴጌ ምንትዋብ ዘመን ደግሞ የህዝብ ብዛቱ እስከ 100 ሺህ ደርሶ ነበር።
ጎንደርን በወቅቱ ከነበሩት የሃገሪቱ አካባቢዎች ለየት የሚያደርጋት ቤተ እስራኤሎች፣ ባህላዊ እምነት ተከታዮች፣ ሙስሊሞች፣ የውጭ ዝርያ ያላቸው ቱርኮች… ሁሉም አንድ ላይ እንደልባቸው ተስማምተው የሚኖሩባት መሆኑ ነበር፡፡ በተለያዩ ሥራዎች ላይ የተሰማሩ የህብረተሰብ ክፍሎችም ይኖሩባት ነበር፡፡ አናፂዎች፣ ግንበኞቹ፣ ሸማ ሰሪዎች፣ የብረታ ብረትና የወርቅ ስራ የሚሰሩ እንዲሁም ነጋዴዎች ሁሉ አንድ ላይ ይኖሩባት ነበር፡፡ በጊዜው ንግዱን በሚገባ ያውቁታል ተብሎ ስለሚታመን ነጋድራሶች ከሙስሊሞች ነበር የሚመረጡት፡፡
አፄ ፋሲለደስ ቤተ-መንግስታቸውን ካሳነፁ በኋላ በዙሪያው ሰባት ቤተ-ክርስቲያኖችን አሰርተዋል፡፡ በየጊዜው ነገስታቱ እየተተኩ ለ120 ዓመታት እጅግ የረቀቀ የህንፃ ግንባታ ጥበብን ሰርተው አልፈዋል፡፡ የጎንደር ስልጣኔ የመጨረሻዋ ንግስት የነበሩት እቴጌ ምንትዋብም የራሳቸውን ቤተ-መንግስትና ቤተ-ክርስቲያን አሳንፀዋል ቁስቋም ትባላለች፡፡
በአጠቃላይ የቤተ መንግስቱ ቅጥር ግቢ 70 ሺህ ካሬ ሜትር ቦታ ላይ ነው ያረፈው፡፡ 12 በሮችም አሉት፡፡ ወደ ቅፅሩ የሚገባው እንደየደረጃውና ማዕረጉ በሚፈቅድለት በር ብቻ ነው፡፡
በኢትዮጵያ ታሪክ ንጉሱ ግብር ካላበላ ምኑን ንጉስ ሆነው ይባል ነበር፡፡ ግብር ማስገበርም አለበት፡፡ ግብር በወርቅ፣ በብር፣ በከብት፣ በአሞሌ፣ በጥይት በመሳሰሉት መልክ ከነዋሪው ይሰበሰባል። ንጉሱ ደግሞ በምትኩ ለታችኛው የህብረተሰብ ክፍል ግብር ሰብስቦ በየጊዜው ያበላል፡፡ ራሶችና መኳንንቶችም በየአውራጃቸው ላለ ህዝብ ግብር ማብላት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ግብር ሲበላ ሰው እንደማዕረጉ ነው የሚቀመጠው፡፡ መጀመሪያ ንጉሱ ይቀመጣሉ፤ ከዚያ ንግስቲቷ ይቀጥላሉ፣ እጨጌውና የአክሱም ንቡረ ዕድ ይከተላሉ፡፡ እንዲህ እንዲያ እያለ መኳንንቱ በየደረጃቸው ይቀመጣሉ፡፡ ብዙውን ጊዜ ከፋሲካ በኋላ ነው ግብር የሚበላው፤ በበአላትም እንደአስፈላጊነቱ ንጉሱ ደግሶ ህዝቡን ያበላል፡፡
ዳኝነት የሚሰጠው እምነትን መሰረት በማድረግ ነበር፡፡ የእምነት ወይም ከፍተኛ ሃገራዊ ጉዳይ ከሆነና በመኳንንቱ መወሰን የማይችል ከሆነም ዙፋን ችሎት ላይ ይቀርባል፡፡ ከፋሲል በኋላ አፄ (ፃድቁ) ዮሐንስ ነበሩ፡፡ እሳቸው የእንስሳትን መብት እስከማስጠበቅ የደረሱ ሰው ናቸው፡፡ ከደግነታቸው ብዛት ትልቅ ደውል በውጭ በኩል አስተክለው ነበር፡፡ ዳኝነት ጎደለብኝ ተበደልኩ የሚል ሰው መጥቶ ይደውላል፡፡ ከዚያም ይገባና ከንጉሱ ዘንድ ፍርድ አግኝቶ ይሄዳል፡፡ አንድ ጊዜ ምን ሆነ፡- ዝናብ እየዘነበ ነበር፡፡ ደውሉ ይደወላል፡፡ በዚህ ዝናብ ማን ፍርድ የጎደለበት ይሆን የመጣው ብለው እልፍኝ አስከልካያቸውን ይልኩታል፡፡ “ኧረ ጃንሆይ አህያ ነው እንጂ ሰውስ የለም” ይላቸዋል፡፡ አህያውን አስገባው አሉት፡፡ አህያው ሲታይ ጀርባው ተጋግጧል፡፡ ባለቤቱ ተፈልጎ ይቅረብ ተባለና መጣ፡፡ “ለምን እንዲህ አደረክ፣ እድሜ ልኩን ያገለገለህን አህያህን ለምን ጣልከው?” ሲሉ ሰውየውን ገስጸው ቀጥተው ላኩት፡፡ አህያው ደግሞ በቤተ መንግስት ውስጥ ገብስና ባቄላ እየበላ እንዲኖርና ከቁስሉ እንዲያገግም ተደረገ፡፡ በዚያውም “የተገጠበ አህያ ጭነት እንዳይጫን” የሚለው አዋጅ ታወጀ፤ ጭኖ የተገኘም ይቀጣ ነበር፡፡ ያኔ ነው የእንስሳት መብት የታወጀው፡፡
ጎንደር ከመመስረቷ በፊት በአካባቢው አራት ደብሮች ነበሩ፡፡ አንደኛው አርባዕቱ እንስሣ ይባላል፡፡ በሌላ አቅጣጫ ቃአ ኢየሱስ የሚባል አለ፡፡ ጊዮርጊስ በሌላ አቅጣጫ አለ፤ አበራ ጊዮርጊስ የሚባልም አለ። ከዚያ በኋላ አፄ ፋሲል 7 ተከሉ፡፡ ፃድቁ ዮሐንስ 2 ተከሉ፣ አድያም ሰገድ ኢያሱ ደብረ ብርሃን ስላሴ ጨምሮ 2 ተከሉ፡፡ እንዲህ እንዲያ እያሉ ነገስታቱ በተፈራረቁ ቁጥር አዳዲስ ደብሮችን ሲተክሉ ኖሩ። በዚህ ሂደት በእነዚህ ነገስታት 30 ተተከሉ። 14 ያህሉ ደግሞ ቀድሞም የነበሩ ናቸው፡፡ እነዚህ ተደምረው ጎንደር የ44 ታቦት መገኛ ሃገር ተባለች፡፡ ኋላ ላይ በደርቡሽ ጦርነት 4 ያህሉ ተቃጥለው ነበር፡፡ ሃገሬው የተቃጠሉትን እንደገና ሰርቷቸው ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ ሌሎች ደብሮች በብዛት የተተከሉ ቢሆንም የጥንቱን የጎንደር ስልጣኔ ለማስታወስ 44ቱ ታቦታት የጎላ ቦታ አላቸው፡፡
በ1960ዎቹ የተፃፈ አንድ ታሪክ የሚያሳየው፤ ፋሲል ቤተመንግስቱን እንደ ኖህ መርከብ አድርጎ እንደሰራው ነው፡፡ ከዚህ ውጪ ያለው ታሪክ የመጣው ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ነው፤ ግን ሰፊና ጥልቀት ያለው ጥናት ይፈልጋል።
የቤተ መንግስቱ የህንፃ ጥበብ ዋናው ነው፡፡ አንዳንዶች የውጭ ሰዎች እጅ አለበት ይላሉ፤ ነገር ግን አሰራሩ በፊትም በአክሱም ዘመነ መንግስት የነበረ ነው፡፡ ህንዳውያንም ሆነ ፓርቹጋሎች ከመምጣታቸው በፊት እንደነበር ይናገራል፡፡ እ.ኤ.አ ከ1563-97 ዓ.ም የነገሱት አፄ ሰርፀድንግል ቤተ መንግስታቸው እንፍራንዝ የምትባል ቦታ (ከጎንደር ወደ ባህርዳር ሲሄድ 60 ከሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኝ ቦታ) ላይ የሚገኝ ቤተ መንግስት ላይ ይህ ቴክኖሎጂ ተሰርቶበታል፡፡ ስለዚህ የውጭ ኃይሎች እጅ አለበት የተባለው አያሳምንም፡፡
ሌላው ግዙፍ የሆኑ የንግድ መስመሮች - እስከ አውሮፓ፣ ኤሽያ የሚዘልቁ ተፈጥረው ነበር፡፡ የቤተ መንግስቱን አኗኗር ካየን ደግሞ ዘመናዊ ነበር፡፡ ዛሬ ፋሽን የምንለው… በዚያን ጊዜ ቀጭን ፈታዮች በሚባሉ ባለሙያዎች ለቤተ መንግስቱ ወይዛዝርት በየአይነቱ አልባሳት እየተሰሩ ያንን ፋሽን ይከተሉ ነበር፡፡ ዛሬ “ስቲም” የምንለው ያኔ “ወሸባ” ይባል ነበር፡፡ የፀጉር፣ የንቅሳት አይነት እንደፋሽን ይታይ ነበር፡፡ ዛሬ ዶሮ አስራ ሁለት ብልት አላት እንላለን። ያ መለኪያ የወጣው በወ/ሮ ምንትዋብ ጊዜ ነው። የዓሣ አሰራርና የተለያዩ የምግብ አሰራሮች ያኔ የመጡ ናቸው፡፡ ይህ ስርአት እንግዲህ ወደ ከተማው ተስፋፍቷል፡፡ እኛ ዛሬ የተጣራ ውሃ እያልን የታሸገ ውሃ እንጠጣለን፡፡ ይሄ በዚያን ጊዜም ይደረግ ነበር። የፈረስ ማቆሚያ (ፓርኪንግ) አገልግሎት ይሰጥ ነበር፡፡ ዛሬ የመኪና ፓርኪንግ እንደምንለው በአፄ በከፋ ዘመን ባለ ዘጠኝ በር ዘመናዊ የፈረስ ማቆሚያ /ፓርኪንግ/ ተሰርቶ ነበር፡፡ እንግዶች ፈረሶቻቸውን እዚያ ነበር የሚያቆሙት፡፡
(የታሪክ ተመራማሪው አቶ ሲሳይ ሳህሌ በጎንደር ታሪክና ሥልጣኔ ዙሪያ ለአዲስ አድማስ ከሰጡንን ማብራሪያ የተወሰደ #habesha #gondarethiopia #history
Доступные форматы для скачивания:
Скачать видео mp4
-
Информация по загрузке: